መዝሙር እና ፖለቲካ
በመዝሙር ብቻ የምናውቀው ደረጀ ከበደ ወንድማችን ዘማሪ ደረጀ ከበደ በፖለቲካና በማህበራዊ ጉዳዮች ላይ አስተያየቱን መሠንዘር ከጀመረ ዓመት ሆኖታል። የፌስቡክ ታዳሚዎቹ፣ "ይኸ እርሱ አይደለም፣ በስሙ የሚነግዱ ግለሰቦች ናቸው" ወይም "ደረጀ እዚህ ዓይነት ውስጥ ባይጠላለፍ መልካም ነው" ወይም “ዶ/ር እንኳን የፌስቡክ ገጽህ ጓደኞች ልንሆን መድረክ ላይ ቆመህ ስታገለግል እንኳን ለማየት” ያልታደልን ነን እያሉ ነው። "እኔ ደረጀ ነኝ" ቢላቸውም፣ "በቪዲዮ ፊትህን አሳየንና፣ ድምጽህን አሰማንና እንጂ አናምንም" ብለዋል። ይኸ ሁሉ የሚያሳየው፣ ደረጀ ዓመታት ነጒደው እንኳ በሕዝብ ዘንድ ያሳደረው ፍቅር አለመደብዘዙን ነው። የእግዚአብሔር ጸጋ እውነትም አያረጅም፣ አያስረጅም! ደረጀ ከጅምሩ፣ “ፖስት የማደርጋቸው አስተያየቶችና ፅሁፎች የማይመቻችሁ ወገኖች ሰላማችሁ እንዳይደፈርስ በፍቅር ራሳችሁን ከገፁ ማግለል ትችላላችሁ” ብሏቸዋል። አባባሉ ግን ጥያቄ ያስነሳል። ለምሳሌ፣ መብትን በፍቅር ስለ መያዝ ምን ይነግረናል? መብት ዕንቅፋት ሲሆንስ? ( 1ኛ ቆሮንቶስ 8፡9 ) በቀደመው ጥሪ ጸንቶ ማገልገል እንዴት ይቻላል? ( 1ኛ ቆሮንቶስ 12 ፤ ራእይ 2፡4፣5 ) ከስደት ዘመን ይልቅ በ “ሰላምና ነጻነት” ዘመን እነዚህን ጥያቄዎች መጠየቅ ግድ ነው። ደረጀ ፈር ቀዳጅ ነው፤ ዓይነተኛ ነው። ይህን በተለየ መንገድ የተረዳሁት ያሳተማቸውን ዘጠኝ አልበሞች በቅደም ተከተል ደርድሬ ለሰዓታት ባዳመጥኩ ጊዜ ነው። ረጅም “የክርስቲያን ጒዞ” እንደ መጓዝ ነው። ከርቀት ኮረብታን እንደ ማየት፣ አልፎ ወደ ኋላ መመልከት። ለምለም ሣር፣ ወንዝ፣ ቀጥሎ ምድረበዳ። ደስታ፣ ግራ መጋባት፤ የጠራ ሰማይ፣ የፀሐይ ሐሩር፣ ዶፍ፣ ነፋስ፣ ጠ...