መንግሥት ተለዋውጦ ሕዝብ የተረሣበት
አገራችን ዓይነተኛ መሪዎች የነበሯት ዘመን ነበር። አገር ወዳድ፤ እግዚአብሔርን የሚፈሩ። ምን ያደርጋል ታዲያ? ትውልድ ይጠይቅ ለነበረው ጥያቄ ቶሎ ምላሽ መስጠት አልቻሉም! ዘገዩ። ከ13 ዓመት በፊት እነ ጄኔራል መንግሥቱ ንዋይ ሞክረው ከከሸፈባቸው የመንግሥት ግልበጣ ምንም አልተማሩም። ከ13 ዓመት በኋላ የባሰ መጣባቸው፤ መንግሥቱ ኃይለማርያም የተባለ ሻለቃ። ሲያዋርዳቸው። እስከ ዛሬ የሚያቃጥለኝ፣ አለህግ አለርኅራኄ መገደላቸው ነው። ከዘውዱ አገዛዝ በኋላ በደርግ ዘመን የተነሡትም የማያሳፍሩ አገር ወዳድ መሪዎች ነበሩ። የቀድሞዎቹ ዘገዩ፤ ያሁኖቹ ተጣደፉ። በጥድፊያ ብዙ አጠፉ። እግዚአብሔርን ናቁ። ያለርኅራኄ ያለፍትኅ ተገዳደሉ። ዛሬ ያለንበት ውድቀት (ከአዲሳባ ዩኒቨርሲቲ ከ2ኛና ከ3ኛ ድግሪ ምሩቃን ብዙዎቹን በንጉሡም በደርግም ከነበሩት ጋር ማስተያየት ጨርሶ የማይታሰብ ነው። ነገሩ ጠ/ሚ ዐቢይ እንደሚሰብኩን አይደለም። አገርን በባዶ ወረቀት/ያለእውቀት፣ በማዕረግና በወዳደቀ ዩኒቨርሲቲ ማልማት ጨርሶ አይቻልም። ሚንስትሩና አብረዋቸው ያሉት ጧት ማታ እንደ ድግምት ብልጽግና ብልጽግና ይሉናል። አገር ለመምራት የበቁ ዜጎችን ማሠልጠን እስካልተቻለ ግን፣ አገራችን የቱሪስት ገንዘብ ማራገፊያ፣ የቱጃር ዐረቦች መናኻሪያ እንኳ ብትሆን፣ ዜጋ ከጫማ ጠራጊነት ከለማኝነት አይወጣም። እህቶቻችን ባልባሌ ሥፍራ ከመዋል ውጭ ለራሳቸውም ላገራቸውም አይበጁም። በገዛ አገር ባእድ መሆን ነው። እነ መንግሥቱ የአፄ ኃይለሥላሴን ስህተት ለማረም ተነሡ። የባሰ አበላሽተው ተወገዱ። እነ መለስ ዜናዊ የአፄ ኃይለሥላሴንም የደርግንም ለማቃናት ተነሡ። የባሰ አንጋድደው፣ ራሳቸውም ተወገዱ። ከእነ መለስ አብራክ የተገኙት ዐቢይ፣ ከ10 ዓመት ንግሥ በኋላ...