ምክክር ምክክር ምክር የማይሰማ ማ ይሆን?
የምክክር ኮሚሽኑ የተጠቃለሉ አጀንዳዎችን በሚቀጥለው ሳምንት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደሚያቀርብ ተገለጸ። የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን የ2018 ዓ.ም ዋና ዋና ክንውኖችና ቀጣይ ሥራዎችን አስመልክቶ ጷጉሜ 5 ቀን 2018 ዓ.ም በሰጠው መግለጫ፣ ዋና ኮሚሽነር መስፍን ዓርአያ (ፕሮፌሰር) የተጠቃለሉ የአጀንዳ የውሳኔ ሐሳቦች መስከረም 10 ቀን 2019 ዓ.ም ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደሚቀርብ ተናገሩ። ይህም የሚሆነው ለተሳናባቾቹ የፓርላማ አባላት ስንብት ከመደረጉ በፊት መሆኑን ተናግረዋል። 400 አጀንዳዎች እየተደራጁ መሆኑን የገለጹት ዋና ኮሚሽነሩ፣ መንግሥት የአጀንዳ ትግበራን የሚከታተልበትን የዕቅድ ስትራቴጂ አስመልክቶ ራሱን የቻለ ምክረ ሐሳብ ለማቅረብ እየተዘጋጁ መሆናቸውን አስረድተዋል። [ሪፖርተር ጋዜጣ በፌስቡክ ገጹ፣ መስከረም 1/2019 ዓም] ኮሚሽኑ ምን ያህል ነፃ እንደ ሆነ ይታያል። የገዥው ፓርቲ ጉዳይ አስፈፃሚ ከሆነም ይታያል። የራሱን ሥራ ሪፖርት መንግሥት ሳንሡር ሳያደርገው በቀጥታ ለሕዝብ ማሠራጨት ይችላል? ያ ካልሆነ ኮሚሽነሩ፣ ፕሮፌሰር መስፍን አርኣያ ሥልጣኔን እለቃለሁ ብለው እንደ ነበር አንርሳ! በሌላ ሥፍራ እንዳመለከትኩት፣ የኢትዮጵያ ችግሯ እርስበርስ አለመተማመን ነው፤ መተማመንን ሳይሆን አለመተማመንን ሥራዬ ብሎ የሚዘራ አመራር መኖሩ ነው!